ሰላማዊ ትግል እና የመለስ ራዕይ ዘር-የማጥራት ወንጀል ስለመሆኑ

(ግርማ ሞገስ)

ethnicity

 

ከጉራፈርዳ እና ከቤንሻንጉል-ጉምዝ የተሰሙት ድምጾች ዘር የማጥራት (Ethnic Cleansing) ወንጀል በኢትዮጵያ ህጋዊ መሆን መጀመራቸውን አስታወቁ። እነዚህ ድምጾች የኢትዮጵያ ፌዲራል መንግስት እና የክልል መንግስቶች ኢትዮጵያን ለመበተን ውስጥ ውስጡን የነበራቸውን የአሳብ እና የተግባር ስምምነት ገሃድ በማውጣት የኢትዮጵያ አንድነት አደገኛ ምዕራፍ ላይ መድረሱን ግልጽ አደረጉ። የኢትዮጵያ አንድነት ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፍ ለሚመኙ አገር ወዳዶች በሙሉ እንቅልፍ የሚነሳ መልዕክት አስተላልፈዋል ከጉራፈርዳ እና ከቤንሻንጉል-ጉምዝ የተሰሙት ድምጾች ። የኢትዮጵያችን ጉዳይ ያገባናል ለሚሉ አገር ወዳድ ዜጎች በሙሉ የኢትዮጵያ ህዝብ የመንግስት ስልጣን ባለቤት እስከሚሆን ድረስ በኢትዮጵያ አንድነት ላይ የተደቀነውን አደጋ ለመከላከል ያልተቋረጠ በድስፕሊን የታነጸ ሰላማዊ ትግል ማድረግ እንዲጀምሩ ጥሪ አድርገዋል እነዚህ ድምጾች። ለመሆኑ ይህ ኢትዮጵያ እዚህ አደገኛ ምዕራፍ ውስጥ መግባቷ መቼ እና እንዴት ተሰማ? አገር ወዳዶችስ ምን ምላሽ ሰጡ?

የኢትዮጵያ አንድነት አደገኛ ምዕራፉ ውስጥ መግባቱ በግልጽ የተረጋገጠው ከጉራፈርዳ (ደቡብ ኢትዮጵያ) በተሰማው የአደጋ ደወል ድምጽ ነበር። ብዙ ቁጥር ያላቸው በጉራፈርዳ ይኖሩ የነበሩ ግብር ከፋይ አማርኛ ተናጋሪዎች በአቶ ሽፈራው ሽጉጤ በሚመራው የክልል መንግስት ወደ አገራችሁ ተመለሱ የሚል ዘር-የማጥራት ወንጀል ሲፈጸምባቸው የፌዴራል መንግስት ህገ መንግስት የበላይ ጠባቂ መሆናቸውን ሲገልጹልን የነበሩት አቶ መለስ ከተፈናቃዮች ለቀረባለቸው አቤቱታ ህገ-መንግስታዊ መልስ መስጠት ሲገባቸው በምትኩ አማርኛ ተናጋሪዎች የተባረሩት አማርኛ ተናጋሪ በመሆናቸው ሳይሆን ጫካ በማንደዳቸው ነው የሚል ማብራሪያ በመስጠት የክልሉ መንግስት የወሰደውን የዘር ማጥራት ወንጀል ትክክለኛ የሚያደርግ ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ነው። የአቶ መለስ ማብራሪያ መልዕክት ባጭሩ የጉራፈርዳ አማርኛ ተናጋሪዎች ወደ አገራቸው መመለስ አለባቸው የሚል ነበር። ጫካ ያነደደ ግብር ከፋይ እዚያው በሚኖርበት ክልል ሆኖ የክልሉ ህግ በሚደነግገው መሰረት ይቀጣል እንጂ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በፈለገበት ክልል የመኖር እና ሃብት የማፍራት መብት እንዳለው የሚገልጸው ህገ-መንግስታዊ መብቱ አይሰረዝም። ይኽ የአቶ ሽፈራው ሽጉጤ ዘር-ማጥራት እርምጃ እና የአቶ መለስ የትብብር ማብራሪያ በኢትዮጵያ አንድነት ብተና ጥያቄ ላይ የክልሉ መንግስት እና የፌዴራል መንግስት የነበራቸውን ውስጠ-ምስጢራዊ የአሳብ እና የተግባር ስምምነት ግልጽ አወጣ። የህውሃት እና የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች (ብእዴን፣ ኦነግ እና የደቡብ ህዝቦች) ግንኙነት የአዛዥ እና የታዛዥ ግንኙነት በመሆኑ ከራዕዩ ባለቤቶች ከህውሃቶች መመሪያ እስካላገኙ ድረስ የክልል መሪዎች ይኽን አይነት ወንጀል በራሳቸው አነሳሽነት አይፈጽሙም። ያም ሆነ ይህ ዘር-ማጥራት (Ethnic Cleansing) አገራዊ እና አለም አቀፋዊ ወንጀል ነው። አቶ መለስ እና አቶ ሽፈራው ዘር-የማጥራት ወንጀል ፈጽመዋል። በህይወት ባሉት በአቶ ሽፈራው ላይ በማንኛውም ጊዜ በአለም አቀፍ ደረጃ ክስ ሊመሰረትባቸው ይችላል። የኢትዮጵያ ህዝብ የመንግስት ስልጣን ባለቤት ሲሆን ደግሞ በኢትዮጵያ ክስ ሊመሰረትባቸው ይችላል። እንደሚታወቀው አንዳንድ ወንጀሎች ከተፈጸሙበት ጊዜ ጀምሮ በተወሰኑ ጊዚያት (አመቶች) ውስጥ ክስ ካልተመሰረተባቸው ወድቅ ይሆናሉ። ዘር የማጥራት (Ethnic Cleansing) ወንጀል ክስ ምስረታ ግን ህጋዊ የዕድሜ ገደብ (Statue of limitation) የለውም። አቶ ሽፈራው ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ሌሎች የህውሃት እና የክልል መንግስት ባለስልጣኖች ጋር እድሜያቸው ከመቶ አመቶች በላይ ቢሆንም ሊከሰሱ ይችላሉ። ቁም ነገሩ ምረጃ ማሰባሰብ ነው።

በመጋቢት 2004 (April 2012) ዓመተ ምህረት ግድም አቶ መለስ እና አቶ ሽፈራው የፈጸሙትን አገራዊ እና አለም አቀፋዊ ወንጀል በሚመለከት የተቃውሞ እና የኩነና መግለጫ ከማተም እና ከማሰራጨት ባሻገር ተራምደን የአጋጅነት አቅም ያለው ተጨባጭ ህጋዊ እርምጃ ባለመውሰዳችን አቶ መለስ ከሞተ ወዲህ ከጉራፈርዳው ዘር-ማጥራት ወንጀል በመጠኑ የላቀ እና በአይነቱም የከፋ ብዙ ሺ አማርኛ ተናጋሪዎችን ያፈናቀለ ዘር-ማጥራት በቤንሻንጉል-ጉምዝ ተደገመ። በዚኽን ጊዜ አቶ ኃይለማሪያም የፌዴራል መንግስቱን ሲመሩ የቤንሻንጉል-ጉምዝ ክልል መንግስት ፕሬዘዳንት ደግሞ አቶ ያሲን አህመድ ናቸው። የሆነው ሆኖ አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝን ጨምሮ የፌዴራል መንግስት ባለስልጣኖች ስለጉዳዩ ሲጠየቁ ጉዳዩ አያገባንም በማለት የቤንሻንጉል-ጉምዝ ክልል መንግስት በፌዴራል መንግስት እንደማይጠየቅ ግልጽ አድርገዋል። ይኽ የፌዴራል መንግስት ባለስልጣኖች መልስ የኢትዮጵያን አንድነት አስመልክቶ ቀደም ሲል በአቶ መለስ ገዢነት ዘመን እንደነበረው ዛሬም በአዲሱ ጠቅላይ ምኒስትር አቶ ኃይለማሪያም ዘመንም በፌዴራል መንግስት እና በክልል መንግስት መካከል የአሳብ እና የተግባር ስምምነት መኖሩን አረጋገጠ። እንግዲህ የኢትዮጵያ አንድነት አደገኛ ምዕራፍ ውስጥ እንደሚገኝ ከዚህ በላይ ማረጋገጫ እንፈልግ ማለት አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይሰማም አይነት ጨዋታ ይሆናል። የሆነው ሆኖ ከፍ ብሎ እንደተገለጸው የኢትዮጵያን አንድነት ማፍረስ ራዕይ የህውሃት መሪዎች በሽታ ነው። ከራዕዩ ባለቤቶች የህውሃት መሪዎች መመሪያ እስካላገኙ ድረስ አቶ ኃይለማሪያምም ሆኑ የክልል መሪዎች ይኽን አይነት ወንጀል በራሳቸው አነሳሽነት አይፈጽሙም። ያም ሆነ ይህ አቶ ኃይለማሪያም ህገ-መንግስት ባላስከበራቸው እና አቶ ናስር አህመድ ደግሞ በቀጥታ ዘር-የማጥራት ወንጀል በመፈጸማቸው ሁለቱ ሰዎች እና ሌሎች በጉዳዩ እጃቸው እንዳለበት መረጃ ሊቀርብባቸው የሚችሉ ሰዎች በህይወት እስካሉ ድረስ መቼም ይሁን መች ክስ ሊመሰረትባቸው ይችላል። መረጃ ማሰባሰብ ግን ቁልፍ ነው።

እንግዲህ እስከዚህ ድረስ እንዳነበብነው በኢትዮጵያ የፌዴራል እና የክልል መንግስት ባለስልጣኖች በሽርክና ዘር-የማጥራት ወንጀል ሊፈጽሙ ይችላሉ። ድርጊቱን በመፈጸም ቀጥተኛ ተሳትፎ ያላቸው የክልል መሪዎች በፌዴራል መንግስት ባለስልጣኖች በሃላፊነት አይጠየቁም። ይኽ ሁኔታ በኢትዮጵያ ተቀባይነት ያገኘ አዲስ የፖለቲካ እውንታ (New Political Normal) ሆኗውል ማለት ነው። ከፍ ብሎ በተደጋጋሚ እንደተመለከተው ለዚህ አዲስ የፖለቲካ እውንታ (New Political Normal) ህውሃትን እና የህውሃትን መሪ አቶ መለስን በዋንኛነት የዘር-ማጥራት ወንጀል አባት አድርጌ ክስ መስርቼባቸዋለሁ። ባጭሩ ላብራራ።

የህውሃት ራዕይ አመንጭ የሆኑት አቶ መለስ ቀደም ሲል በ1976 ግድም (?) የትግራይ ሩፓብሊክ መመስረት ራዕያቸውን ተፈጻሚ ለማድረግ የጻፉት የመጀመሪያ ፕሮግራም ትግራይን በትጥቅ ትግል ከኢትዮጵያ መገንጠል የሚል እንደነበር እናውቃለን። ያን ፕሮግራም የያዘው ሰነድ ዛሬም ለታሪክ አለ። ይሁን እንጂ ያ ፕሮግራም ከውስጡ ትግራይን ከኢትዮጵያ መገንጠል የሚለው አንቀጽ እንዲወጣ ተደርጓል። ምክንያቱም በአቶ መለስ እና በእነ ስዩም መስፍን አይነቱ ሸሪኮቻቸው ዘንድ በድንገት የኢትዮጵያ አንድነት ፍቅር ሰፍኖ ወይንም የኢትዮጵያን አንድነት አምነውበት እና የቀድሞ አሳባቸውን በሃቅ ቀይረው ሳይሆን በወቅቱ በህውሃት ውስጥ የነበሩ አፍቃሪ ኢትዮጵያ የትግራይ ተወላጆች መገንጠልን በመቃወማቸው ነበር። በግዳጅ ውድቅ ማድረግ የሚቻለው በወረቀትላይ የተጻፈ የራዕይ ማስፈጸሚያ ፕሮግራምን ሊሆን እንደሚችል በእርግጠኛነት መናገር እንችላለን። ስለዚህ አፍቃሪ ኢትዮጵያ የትግራይ ትወላጅ የሆኑት የህውሃት አባላት በመገንጠል ጥያቄ ላይ ባነሱት ተቃውሞ የተነሳ እነ አቶ መለስ ተገደው አፈገፈጉ ማለት እንችላለን። ይሁን እንጂ በእነ አቶ መለስ ጭንቅላት ውስጥ የነበረው ራዕይ ከፕሮግራሙ ጋር አብሮ ውድቅ ሆኗል ብለን በእርግጠኛነት መናገር ግን አንችልም። እንግዲህ የእነ አቶ መለስ የመጀመሪያ ፕሮግራም ትግራይን በቅድሚያ በመገንጠል የትግራይ ሩፓብሊክ በመመስረት ኢትዮጵያን ማፍረስ ነበር። ይሁን እንጂ በተደረገው የፕሮግራም ለውጥ የተነሳ እነ አቶ መለስ (ተገደው ማለት ነው) የኢትዮጵያ ገዥ ለመሆን መታገልን ተቀበሉ። ይኽም መንገድ ቢሆን ከመርዘሙ እና ብዙ አጭበርባሪ ስራዎች ከመጠየቁ በስተቀር የትግራይ ሩፓብሊክ መመስረትን የማይቻል ጉዳይ እንደማያደርገው ግልጽ ነው። ይኽን መገንዘብ ለእነ አቶ መለስም አያዳግትም። ይኽ እንግዲህ የመንግስት ስልጣን ከመጨበጣቸው በፊት የነበረው ሁኔታ ነበር። የመንግስት ስልጣን ከጨበጡ በኋላስ?

አቶ መለስ የኢትዮጵያ መሪ በነበሩባቸው የመጀመሪያ አስር አመቶች ውስጥ ማለትም እንደነ ስየ አብርሃ፣ እነ አስራት ገብሩ አይነቶቹ አፍቃሪ ኢትዮጵያ የህውሃት አባላት ህውሃት እና በመንግስት ስልጣን እስከነበሩበት ጊዜ ድረስ አቶ መለስ ኢትዮጵያን የማፍረስ ራዕያቸውን (የትግራይ ሩፓብሊክ ምስረታ) በ1976 (?) ግድም ከደበቁበት ማውጣት እና በይፋ መፈጸም ሊያዳግታቸው እንደሚችል መገመት አያዳግተንም። አቶ መለስ አመቺ ሁኔታ የተፈጠረላቸው የኢትዮ-ኤርትራን ጦርነት አፈጻጸም አስመልክቶ የማላምንበትን ጦርነት እንድመራ ተደርጌያለሁ ማለት ከጀመሩበት ጊዜ ጀምሮ በጦርነቱ ልዩ ልዩ ጉዳዮች ላይ ከእነ ስየ አብርሃም ጋር ልዩነታቸው እያደገ ሄዶ በመጨረሻ እነስየ አብርሃ፣ እነ አስራት ገብሩ እና የመሳሰሉት በህውሃት ውስጥ የነበሩት አፍቃሪ ኢትዮጵያ አባላት ከድርጅቱ እና ከመንግስት ከለቀቁ በኋላ ነበር። ከዚያ በኋላ አቶ መለስ በህውሃት ውስጥ ተው ባይ አልነበረውም ነበር። በኢህአዴግም ውስጥ ቢሆን አራቱ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች መሪዎች የመለስ የመለስ ውለታ ስላለባቸው ከታዝዥነት ያለፈ ሚና አልነበራቸውም። በዚህን ጊዜ በህውሃትም ሆነ በኢህአዴግ ወስጥ ተው ባይ አልነበረውም። የምርጫ 97 አፈጻጸም ደግሞ ተጨማሪ ገጸ በረከት ስለሆነለት አቶ መለስ በኢትዮጵያ ላይ ግለሰባዊ አምባገነንነቱን ተከለ። ስለዚኽ አቶ መለስ ኢትዮጵያን የመበተን ራዕዩን (የትግራይ ሩፓብሊክ ምስረታ ናፍቆቱን) በ1976 (?) ግድም ከቀበረበት ቆፍሮ አውጥቶ የመንግስት ፕሮግራም ሊያደርግ የሚችለው (የቻለው) በዚኽን ጊዜ ነበር ብንል ብዙም ስህተት አይሆንም።

ይሁን እንጂ ረዥም እድሜ ያላትን እና በአለም ህብረተሰብ ታዋቂ የሆነች ኢትዮጵያን እየገዛ ማፍረስ ቀላል ስለማይሆን አቶ መለስ አጭበርባሪ ፕሮግራሞችን የቀየሰ ይመስላል። “ኢትዮጵያን የማፍረስ” ፕሮግራሙን “ኢትዮጵያን መገንባት” በሚል ሸፈነው። በዚህን ጊዜ አቶ መለስ አብዮታዊ ዲሞክራሲ የኢትዮጵያ መመሪያ እንደሆነ ገለጸ። የብሄር ብሄረሰብ እና የባንድሪዋች በአላትም ደነገገ። “ርሃብን በኢትዮጵያ ማጥፋት”፣ “አገር ማልማት” “የባቡር ሃዲድ መዘርጋት”፣ “ህንጻ ግንባታ”፣ “አዲስ አበባን አፍርሶ መገንባት” በተባሉ አጭበርባሪ ፕሮጀክቶች የኢትዮጵያን ህዝብ ቀልብ ሲስብ የለጋሽ አገሮችን አድናቆት አገኘ። እርዳታ ጠየቀ፣ አገኘ። የግብጽ ሰላማዊ አብዮት ሲመጣ ደግሞ አቶ መለስ ድንገት ተነስቶ “የአባይ ግድብም ጥናት” ተጠናቁዋል በማለት አባይን በግንባታ ዝርዝር ውስጥ ከተተው። በአንድ በኩል ይኽ ሁሉ በኢቲቪ ካለማቋረጥ ሲሰበክ በሌላ በኩል ደግሞ ዜና እና መረጃ ከውጭ ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡባቸው ቀዳዳዎች እየተፈለጉ ተደፈኑ። ቪኦኤ፣ ጀርመን ሬዲዮ ታፈኑ። ድረ-ገጾች ተጋረዱ። ባጭሩ አቶ መለስ ግለሳባዊ አምባገነንቱን በኢትዮጵያ ላይ ተከለ። ይሁንና “ኢትዮጵያን የመገንባት ፕሮግራም” ከጎኑ ዛሬ ዘር-ማጥራት ወደሚፈጸምባት ኢትዮጵያ መጉዋዝ ማለትም እንደሆነ አንባቢ ያስተውላል። ያም ሆን ይህ የኢትዮጵያን እና የአለምን ህዝብ በማጭበርበር ረገድ እነዚህ አጭበርባሪ ድራማዎች ለጊዜው ሰርቶለት ነበር። በህዝብ ዘንድ ብቻ ሳይሆን በተቃዋሚው ዘንድም ብዥታን ፈጠረ። ስለዚህም አዲስ አበባ ተለወጠች የሚል ውይይት እና ክርክር ተጀመረ። በሰል ያሉ ወገኖች ደግሞ ስልጣን ላይ እስካለ ድረስ እንኳን አዲሳ አበባን መገንባት ሌላም እንዲሰራ ማበረታታ አለብን ነገር ግን በግንባታ ፕሮፖጋንዳ የሸፈነውን መርዝ (የአገር አንድነት ማዳከም) መጋት የለብንም በማለት አጥብቀው አስገነዘቡ። ወዲያውኑ ከአፋር፣ ከጅጅጋ የመፈናቀል ዜናዎች መሰማት ጀመሩ። ከጉራፈርዳ የወጣው አንድ ቋንቋ ተናጋሪን ህዝብ የማጥራት ዜና እና አማርኛ ተናጋሪዎች የተባረሩት አማርኛ ተናጋሪ በመሆናቸው ሳይሆን ጫካ ስላነደዱ ነው የሚለው መፈናቀልን የሚፈቅድ ማብራሪያ ሲደመሩ አቶ መለስ በ”አገር ግንባታ” ጠቅልለው አገር የማፍረስ የቀድሞ ራዕያቸውን ተፈጻሚ ሲያደርጉ ነበር የሚል ግብት በብዙዎች ዘንድ አሳደረ። ቤንሻንጉል-ጉምዝ ደግሞ ጉራፈርዳን በከፋ መልኩ በመድገም የኢትዮጵያ አንድነት የሚገኝበትን አዲስ አደገኛ ምዕራፍ ገሃድ አወጣ። ስለዚህ እስከዚህ ድረስ በዘረዘርኳቸው ምክንያቶች የተነሳ በጉራፈርዳ እና በቤንሻንጉል-ጉምዝ ለተከሰቱት የዘር-ማጥራት ወንጀሎች አቶ መለስን የጭንቅላት አባታቸው ማድረጌ ስህተትነት ያለው አይመስለኝም። የሆነው ሆኖ በጉራፈርዳ እና በቤንሻንጉል-ጉምዝ የተጀመረው ዘር-የማጥራት አደገኛ ምዕራፍ ምን ደረጃ እንደደረሰ ለጥቀን እንመልከታለን።

ዛሬ በኢትዮጵያ በመካሄድ ላይ የሚገኘው ዘር-የማጥራት ወንጀል በፌዴራል እና በክልል መንግስቶች ቅንብር የሚፈጸም ነው። እስከዚህ ድረስ የወንጀሉ ባለቤቶች እነሱ ብቻ ናቸው። ዛሬ ዘር-ማጥራት ፖለቲካ ህዝቡ ውስጥ ገና አልገባም። አማርኛ ተናጋሪው መፈናቀሉን የክልሉ ቀሪ ህዝብ ደግፎ ሲጨፍር እና በተፈናቃዮች ላይ ድንጊይ ሲወረውር አላየንም። ይሁን እንጂ የክልሉ ህዝብ በክልሉ መንግስት ተግባር ተቆጥቶ ሰላማዊ ሰልፍ ወይንም በሌሎች ሰላማዊ መንገዶች የክልላቸው መንግስት የሚፈጽመውን እንደማይተባበርም ሲገልጽ እና እርምጃውን ሲያቆምም አላየንም። የፌዴራል እና የክልል መንግስቶች ባለስልጣናት ግን እራሳቸውን ከተጠያቂነት ለማራቅ ካላቸው ጽኑ ምኞት የተነሳ ዝቅተኛ ካድሬዎችን ሳይቀር የወንጀሉ ባለቤቶች ከማድረግ ወደ ኋላ እንደማይሉ መገመት አያዳግትም። የዚህን አደገኛ ምዕራፍ ግስጋሴ ለመግታት መረጃ መሰብሰብ ቁልፍ ከሆኑ ጉዳዮች ውስጥ ዋንኛው መሆኑ መዘንጋት የለብንም። እንዲሁም የፌዴራል እና የክልል መንግስቶች ባለስልጣናት ህዝቡን የወንጀሉ ባለቤት በማስመሰል እራሳቸውን ከተጠያቂነት ለማዳን በካድሬዎቻቸው አማካኝነት በመዋቅር በሚተላለፍ ትዕዛዝ ህዝቡ የዘር ማጥራቱን ወንጀል የደገፈ ለማስመሰል የድጋፍ ሰልፍ እንዲወጣ ለማድረግ ሊሞክር ይችላል። ያም ሆነ ይህ የተጀመረው አደገኛ ምዕራፍ ወደ ኋላ መመለስ ከማይቻልበት ደረጃ ደርሷል ማለት ያዳግታል። ያን ማለት የምንችለው ህዝቡ በዘር-ማጥራቱ አምኖበት በራሱ አነሳሽነት መሳተፍ ሲጀምር ነው። ይኽን መሰል ሁኔታ በኢትዮጵያ እንዲከሰት ለማድረግ የፌዴራል እና የክልል መንግስቶች ተዓምር ሊሰኝ የሚችል የፖለቲካ ስራ መስራት ያለባቸው ይመስለኛል። ይሁን እንጂ ንቀናቸው እጃችንን አጣምረን መቀመጥ ፍጹም የለበንም። ለማንኛውም በየክልሉ በክልል መንግስቶች የሚፈጸሙ እንቅስቃሴዎችን እንደ ቆቅ በንቃት መከታተል እና በሰነድ መልክ እያዘጋጁ አስተማማኝ ቦታ ማኖር እና ቅጂውን ወደ ውጭ እንዲወጣ በማድረግ በኢትዮ-ሚዲያ እና ሌሎች ድረ-ገጾች ለቪኦኤ፣ ጀርመን ሬዲዮ እና ኢሳት ዘንድ እንዲደርሱ በማድረግ ህዝብ እንዲያውቃቸው ማድረግ ቁልፍ ነው። ይሁንና በቅርብ በፖለቲካው መድረክ ላይ ብቅ ያሉት አቶ ኃይለማሪያም ለረጅም ጊዜ በፖለቲካ መድረክ የቆዩ እና አቶ መለስን ለስልጣን ያበቁ በርካታ የህውሃት አባላትን ቀድመው እንዴት የዘር-ማጥራት ወንጀል ባለቤት ለመሆን በቁ? የህውሃት መተካካት ተንኮል (Setup) ወይንስ አጋጣሚ?

በመተካካት ሽፋን በቅርቡ ኢትዮጵያን የመበተን ራዕይ ከአቶ መለስ ጋር በቅርብ ይጋሩ የነበሩት ነባር የህውሃት 9 መሪዎች ከህውሃት መድረክ ሲወርዱ አይተናል። ይኽን ያደረጉት የወዳጃቸው የአቶ መለስ ራዕይ በአቶ ኃይለማሪያም እና በኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ሊፈጸም እንደሚችል እርግጠኛ በመሆናቸው ነው? እራሳቸውን ከተጠያቂነት ለማራቅ ጊዜው አሁን ነው በሚል ነው ህውሃትን የለቀቁት? የሆነው ሆኖ የህውሃት/ኢህአዴግ መተካካት ግልጽ የሆነ መስፈርት የለውም። ቀደም ሲል ስለመተካካት ሲወራ የነበረው በትጥቅ ትግል የተሳተፉትን እና በእድሜ የገፉትን በትጥቅ ትግል ባለተሳተፉ ወጣቶች መተካት የሚል ነበር። በቅርቡ አቶ ገብሩ አስራት (በቪኦኤ መሰለኝ) ሲያብራራ እንደሰማሁት እና እኔም እንደታዘብኩት ዛሬ እየተፈጸመ የሚገኘው መተካካት ቀደም ሲል ይባል የነበረውን ይጻረራል። በትጥቅ ትግል የተሳተፉ እና በእድሜ የገፉ ቀደም ብለው ስልጣን የለቀቁ ሰዎች ወደ ስልጣን ሲመለሱ እናያለን። በትጥቅ ትግል የተሳተፉ እና በእድሜ የገፉ ዛሬም ቢሆን በስልጣን ላይ የሚገኙ አሉ። የሆነው ሆኖ አቶ ኃይለማሪያም በመተካካት ስም የዘር-ማጥራት ወንጀል ባለቤት ለመሆን እንደበቁ እናስተውላለን። ይሁን እንጂ የቀድሞ መሪያችንን ራዕይ ተፈጻሚ እናደርጋለን የሚለው መሃላ ወንጀለኛ የሚያደርግ አደገኛ መሃላ (መፈክር) እንደሆነ አቶ ኃይለማሪያም ይገነዘቡት አይገንዘቡት ግልጽ አይደለም። ቤተ ዘመድ የሆኑ የቅርብ ሰዎቻቸው እና የቅርብ መካሪዎቻቸው አቶ ኃይለማሪያም ኢትዮጵያን ወደ መጨረሻ ምዕራፍ የሚወስድን ዘር-የማጥራት አደገኛ ጉዙ እየመሩ መሆናቸውን እንዲያስተውሉት ቢያደርጉዋቸው የሚጠቅማቸው ይመስለኛል። በተረፈ በአገር ውስጥ እና በውጭ የምንገኝ አገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን ምን ብናደርግ ይበጃል?

1)  የኢህአዴግ አባላት፣

የብእዴን፣ የኦፕዲኦ፣ የህውሃት፣ በአቶ ኃይለማሪያም የሚመራው የደቡብ ህዝቦች ድርጅት አብዛኛው አባላት አመኑበትም አላመኑበት፣ አወቁትም አላወቁት በኢትዮጵያ በሚካሄደው ዘር-ማጥራት ወንጀል ላይ የተባባሪነት ማህተማቸውን እያኖሩ ነው። ከእነዚህ ድርጅቶች መሪዎች ጋር ባይሆንም በተለይ ከመካከለኛ የድርጅት መዋቅር አንስቶ እስከ ተራ አባሎቻቸው ጋር ትብብራቸውን እንዲነፍጉ ቀና እና የሰለጠነ ውይይት ቢደረግም ይጠቅማል።

2)  የጉራፈርዳ እና የቤንሻንጉል-ጉምዝ ተፈናቃዮች፣

ተፈናቃዩ የአማርኛ ቋንቋ ተናጋሪ ህዝብ የተፈጸመበት ወንጀል በመንግስት እንጂ በህዝብ እንዳልሆነ መገንዘብ ይኖርበታል። በተፈናቀለበት ክልሎች ውስጥ በሚኖረው ህዝብ ላይ ቅር መሰኘት የለበትም። ህዝብን ከህዝብ በማቃቃር እና በማጋጨት የፌዴራል (ህውሃት በዋንኛነት) እንዲሁም የክልል መንግስት የዘር-ማጥራት ወንጀል ባለቤትነትን ወደ ህዝብ (በተለይ ወደ አማርኛ ተናጋሪው) ለማሸጋገር ከፍተኛ ምኞት ሊኖረው ይችላል። የመንግስት ባለስልጣኖች መኞታቸውን ፍጹም እንዳያገኙ ማድረግ አለበን። በአማራው ክልል ውስጥ በሚኖሩ የተለያዩ ቋንቋ ተናጋሪ ህዝቦች ላይ የማፈናቀል እና ዘር-የማጥፋት ወንጀል እንዳይፈጸም አማርኛ ተናጋሪው ነቅቶ መጠበቅ አለበት። የአማራ ክልል መንግስት በልማት ወይንም በሌላ ሽፋን በአማርኛ ተናጋሪው ላይ የተወሰደው አይነት እርምጃ በአማራው ክልል ኑዋሪ ሌላ ቋንቋ ተናጋሪዎች እርምጃ እንደሚወስድ ከተረጋገጠ እንደሙስሊም ወንድሞቻችን በድስፕሊን የታነጸ ሰላማዊ ትግል በማድረግ የመንግስትን እቅድ አማርኛ ተናጋሪው እንደማይደግፍ በገሃድ እና በከፍተኛ ድምጽ ማስታወቅ አለበት። ስለዚህ በጉራፈርዳ እና ቤንሻንጉል-ጉምዝ በአማርኛ ተናጋሪው ላይ የተፈጸመው መፈናቀል እና ዘር-ማጥራት በአማራው ክልል ውስጥ በሚኖሩ ትግሪኛ፣ ኦሮምኛ፣ እና ሌሎች ቋንቋዎች ተናጋሪዎች ላይ እንዳይፈጸም አማራው ዘብ መቆም አለበት። በእነ በረከት ሲሞን የሚመራው ብእዴን የሚያዋቅረው የአማራው ክልል መንግስት ዝምድናው ከአማራው ህዝብ ሳይሆን ከህውሃት መሆኑ ለአፍታም ቢሆን መዘንጋት የለበትም። ወዳጅ መስለው በሚቀርቡ ካድሬዎች ሳይቀር የአማራው ህዝብ የበቀል ግጭት እንዲፈጽም ማግባባት ሊፈጸም እንደሚችል ከጥርጣሬ ውጭ ሊደረግ አይገባም። “በሰፈሩት ቁና መስፈር ይገባል” የሚለው አነጋገር እና እምነት አሳሳች ነው። ይኽ ማለት ግን አማርኛ ተናጋሪው የሚፈጸሙበትን ወንጀሎች የኢትዮጵያ ሙስሊሞች እንዳደረጉት ፍጹም በድስፕሊን የታነጹ ሰላማዊ የትግል ዘዴዎች ተጠቅሞ መብቱን አያስከብር ማለት አይደለም።

3)  የሃይማኖት መሪዎች እና አማኞች፣

በኢትዮጵያ የተለያዩ ክልሎች ውስጥ የሚገኙ የሃይማኖት መሪዎች እና አማኞች ህዝብን ከሚኖርበት አካባቢ ማፈናቀል እና ዘር-ማጥራት እግዚአብሔርም ሆነ ምድራዊ ህግ የማይቀበላቸው ወንጀሎች ስለመሆናቸው በጸሎት ቤትም ሆነ በሌሎች መድረኮች ላይ አጥብቀው መስበክ አለባቸው። የሃይማኖት ተቋሞች የመንግስት መሳሪያ እንዳይሆኑ የሃይማኖት መሪዎች እና አማኞች በንቃት መከታተል አለባቸው። ከኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች መማር አለብን። መንግስት ጣልቃ ሲገባብን ፍጹም በድስፕሊን የታነጹ ሰላማዊ የትግል ዘዴዎች በመጠቀም መቃወም መቻል አለብን። መንግስት አንድ ቋንቋ ተናጋሪን ህዝብ ለማፈናቀል እና ዘር-የማጥራት ወንጀል ለመፈጸም እቅድ እንዳለው ሲታወቅ በክልሉ የሚገኙ የሃይማኖት መሪዎች እና አማኞች ድርጊቱን በአደባባይ በግልጽ መርገም አለባቸው። በሰላማዊ መንገድ ከመንግስት የማፈናቀል እቅድ ጋር እንደማይስማሙ ቢያስታውቁ ጠቃሚ ነው።

Posted by Hellen Tesfaye

Leave a comment