ኣይጋ – ለአውራምባ አቀበለው – አውራምባ ደግሞ- ለትግራይ ኦንላይን!

ሃምሌት ጸጋዬ / በርገን ኖርዌይ

ዑደቱ እንዲህ ይዞራል፡፡ ተረቱም እንዲህ ተለውጧል! «ትንሽ አሻሮ ይዘህ ከቆሎ ተጠጋ»፡፡ ወያኔን  ትንሽ እምት! እምት!  ትንሽ ቦጨቅ፥ ቦጨቅ፡፡ ከዚያም ተቃዋሚ መባል፡፡ ከተቃውሞው አምባ አድብቶ ገብቶ ደግሞ ቀበሮ  መሆን፡፡ ከዚያም እይጋ እየቆነጸለ የሚያወጣውን ትንሽ ለወጥ አድርጎ በአውራምባ ታይምስ ላይ ማውጣት፡፡ ገረብ ገረብ ትግራይ! መቃብረ አምሃራይን በተዘዋዋሪ አጠይሞ ማጮኽ፡፡

ከባለቤቴ ጋር ሆነን የአውራምባውን ዳዊት ከበደን የአከረባበት ስልት አንስተን ስንጨዋዋት ! እኔ ዳዊትን የገመገምኩባቸውን ነጥቦች ባለቤቴ በከፊል ተቀብሎ፣ ላይሆኑ ይችላሉ ያላቸውንም ነጥቦች አነሳሳልኝ፡፡ ዳዊት ወያኔ ሊሆን አይችልም አለኝ መሬት በደንብ ቆንጥጦ፡፡ ለምን አይሆንም አልኩት? ከቅንጅት መሪዎች ጋር አብሮ ሁለት አመት ታስሮ አለኝ፡፡ ብዙ ጊዜ ዞምቢዎች ያሞኙሃል አልኩት፡፡ የባለቤቴን የዋህነቱን ስለማቅ!

የዶክተር አረጋዊ በርሄን መጽሃፍ አንብበህ የለ? ወያኔ እኮ የጦርነት ልብሳቸውን አስወልቆ፣ ኮበሌዎቹን የመነኩሴ ልብስ አስለብሶ ዋልድባ የከተተ መንግሥት ነው፡፡ ለዓላማቸው ቋርፍ እየበሉ፣ ቀኑ ሲደርስ ዋልድባን ያሳረሱት እኮ የወያኔ መነኩሴዎች ናቸው፡፡ ይህ እንዴት ተዘነጋህ ? ለዚያውም ገዳም ውስጥ ሃያ አንድ አመት ችሎ መክረም የሚችሉ ናቸው እንኳን ቃሊቲ ሁለት ዓመት አልኩት፡፡ ለዓላማህ ስትል ቃሊቲ ሁለት ዓመት ብትታሰር ምንድነው? ለዚያውም ጥሩ ጥሩ «ኡፋ» እየጠለፍክ አልኩት፡፡

አቶ መለስ በህይወት ሳሉ፣ መግለጫ ለመስጠት ጋዜጠኞች ሲጠሩ፣ ከግል ፕሬሱ በተለይ ትምክህተኛና፥ ነፍጠኛ የሚባሉት እንዳይገቡ ሲደረግ፣ የዳዊት አውራምባ ግን ዳዊትን ለብሳ ቤተመንግሥት ትገባ ነበር፡፡ መግባቷ አይደለም አቶ መለስና ዳዊት የሚሰሩት ፊልም ነበር፡፡ ዳዊት ጥያቄ ሊጠይቅ እጁን ሲያነሳ፣ መለስ ከእግር  እስከራሱ ዳዊትን በአይናቸው ያነሱታል፡፡ በአድዋኛ ኮድ መሆኑ ነው፡፡ ዳዊት ተቃዋሚ ትግሬ ሆኖ በተቃዋሚዎች ዘንድ ይመዘገባል፡፡ተመዝግቦም  ለሽልማት ታጭቷል፡፡ ያኔ ትዝ ይለኛል፣ የዋህ ኢትዮጵያውያን  በምድረ አሜሪካ ዳዊትን በክብር አጅበው፣ ታላቅ ግብዣ እያደረጉለት! እባክህ ዳዊት አትመለስ! አይምሩህም እነኝህ ሰዎች! እዚሁ ቅር ቢሉት! ኧረ እንዴት ተብሎ! በምንም አይነት ስደት! እዚያው ታግያቸው እሞታለሁ ብሎ ወደ አዲስ አበባ፡፡

አድባር ትከተልህ ብሎ ወገኑ እያዘነ ሸኘው ፡፡ ተቃዋሚዎች አንጀት ውስጥ ዳዊት ተጎዘጎዘ ፡፡ ተጎዝጉዞም አልቀረ ! በብዙም ታመነ ፡፡ ዉብሸትና ዳዊት እዚያችው አውራ አምባ ቢሯአቸው ውስጥ በየክፍላቸው የተነሱት ፎቶግራፍ አለ፡፡ውብሸት ታዬ ፣ እውነተኛዋን የጥንት የጠዋቷን ሰንደቅ ዓላማችንን ቢሮው ጠረቤዛ ላይ ዠቅ አድርጎ አስቀምጧታል ፡፡ዳዊትም እዛው አውራ አምባ ቢሮው ውስጥ የወያኔዋን ባንዲራ ጠረቤዛው ላይ ቀስሯታል ፡፡ ፎቶ ይናገራል ይሏችኋል እንዲህ ነው ፡፡ ካንድ ቢሮ ሁለት ዓይነት ሰንደቅ ዓላማ ፡፡

የውብሸት ጽኑ አቋም እየተለካ ! ለሚፈለገው አካል ተላልፏል ማለት ነው ፡፡ ምስኪኑ ውብሸት ታዬ በጽኑ አቋሙ ፣ እንደነ አንዷለምና እስክንድር ነጋ ተገምግሞ ወደ ዘብጥያ ወረደ ፡፡ የወርቁ ዘር ባለመሆኑ ለርሱ የሚሳሳ አንጀት ወያኔ የለውምና ፣ ሕጻን ልጁን በወጉ እንደ አባት ሳያሳድግ ፣  ያም አነሰው ብለው ሰሞኑን ደግሞ ወደ ዝዋይ ወርወሩት ፡፡

ዳዊት ከቃሊቲ እስር በኋላ ፣ ቀድሞ ያሳትማት የበረቸውን አውራ አምባ እንደገና እንዲያሳትም ፍቃዱ ሲታደስለት ፣ አብርው ከርሱ ጋር የታሰሩት፣ ሲሳይ አጌናና ፥ እስክንድር ነጋ ግን ንብረታቸው ተወርሶ ፥ ገንዘባቸውም ተነጥቆ ፣ጋዜጣ በማሳተም ዙርያ ድርሽ እንዳይሉ ፣ በህገ አራዊት ተከለከሉ ፡፡

ተረቱ አሁንም ተለውጧል ፡፡ ዘመደ ብዙ ጠላው ቀጭን ነው የሚለው ተረት፡፡ እንዲህ ተለውጧል፡፡ « ዘመደ ብዙ መንገዱ ቀጭን ነው » አክተር አይሞትም አይደል ? አክተርማ ከሞተ ፊልሙም ይደብራል ፡፡ የወያኔ ደህንነቶች ፥ ለወርቁ ዘር ልጅ እንዲህ ብለው መከሩት ፡፡ ጎልያድ የሚባለው ኩይሳ አውሬ ሊበላህ ነውና ፣ የቁጩ ወንጭፍህን እጥፍጥፍ አድርግና ማታ በሚነሳው አውሮፕላን ተነስተህ ዋሽንግተን ዲሲ ግባ ፡፡ እዚያም ገብተህ ለተወሰነ ጊዜ አድብተህ ተቃዋሚዎች ጋር ክረም ፡፡ የነብስ አባትህንም መንግሥት ትንሽ  አማ ! አማ ! አድርግ ፡፡ ከቻልክም ኢሳት ላይ ቃለመጠይቅ አድርግ ፡፡ ድረ ገጽህም ሲመረቅ ነውጠኞቹን የአሜሪካ ፋኖዎች ፣ በምርቃቱ ላይ እንዲገኙልህ ጋብዝ ያን ግዜ የተሰጠህን መክሊት ፣አትርፈህባታልና አንተ ታማኝ ባርያ ሞገስና ክብር ከውሀት ታገኛለህ ተብሎ ትመረቃለህ፡፡  ከርምረም ብለህ ደግሞ አጣጥፈህ የወጣሃትን ወንጭፍህን ዘረጋግተህ  ነውጠኞቹን  ቀድብ ተባልክ፡፡

  «ሁሉም በየነገዱ ቢባል ቁርበት የት ሄዶ ተሠለፈ ነው የሚለው ተረቱ » ? ጠፋኝ ! ኢሳት ! የህወሃት ልጆችን    የስልጣን ቦታ በደንብ በተጠና ጥናት የቱን የቱን መሥርያ ቤት እንደተቆጣጥሩ በግልጽ ያሳየው ዜና ጎረበጠህ ፡፡ አልወደድከውም  ፡፡ እያደርክ በኢሳት ላይ የጥላቻ ፍላጻህን ታወርድ ጀመር ፡፡ የአማራው ብሄር በግፍ ሲባረር ምንም ትንፍሽ ያላልከው ሰው ፣ ኢሳትን ከእግር እግሩ እየተከታተልክ ማጥቃት ጀመርክ ፡፡ ስለግንቦት ሰባት አያገባኝም ፡፡ምናልባት የግንቦት ሰባት አባል መስዬህ እንዳይመስልህ ፡፡ ስለ ግንቦት ሰባት አባላቶቹ ሊመልሱልህ ይችላሉ ፡፡ አይደለሁም ፡፡ ግን በኢሳት ላይ አትምጣብኝ ፡፡ ኣይጋ የሚያቀብልህን አንተ ደግሞ ለትግራይ ኦን ላይን በማቀበል በዑደት ዙርያ የምታጠቁት ፣ ገረብ ገረብ ትግራይ ብቀላ የተነቃ ይመስለኛል ዳዊት ! ፡፡

እውነት ተሸፋፍና አትቀርም ፡፡ እስክንድርም ሆነ ዉብሸት አንድ ቀን በህይወት እስካሉ ድረስ ከእስር መውጣታቸው አይቀርም ፡፡ ግን ዳዊት ! ለንስሃ ቀኑ አልመሸም ፡፡ አማራውም እንደ ትግራይ ህዝብ ! ህዝብ ነው ፡፡ ለአማራውም ህዝብ ጩኽለት ! በደሉን በድረ ገጽህ አሰማለት ፡፡ማንም አንተን በትግራዋይነትህ ያገለለህ የለም ፡፡ ይቺ ጨዋታ ናት ! ትልቁ የህውሃት አድባር አልፈዋል ፡፡ምንም እንኳ ራዕያቸው በርሳቸው ደቀ መዝሙሮች ውስጥ ቢቀጥልም ፣ አንተ ግን ከራዕዩ መንፈስ ለመላቀቅ እንድሉ ስላለህ በየቀኑ ስህተቶችን አትደራርብ ፡፡ የሚገርመው ኢሳትን በወቀስክበት ጽሁፍህ አስተያየት የሚሰጡትን ሰዎች የደረደርካቸውን ስሞች ብናይ ! ሁሉም የኦሮሞ ስሞችን የያዙ ማድረግህ ራሱ ሌላ ጨዋታ እንደቀጠልክ ነው የሚያሳየው ፡፡ እነ ገብራይ ስማቸውን ለውጠው እነ ቶሎሳ ሆነው ሲመጡ ሳይ አይጋ ላይ በይቀኑ በኦሮሞ ስም የሚጽፉት ወያኔዎች ትዝ አሉኝ ፡፡

posted by Hellen Tesfaye

Leave a comment